×
ይህ ፅሁፍ ስላት የተወ (የማይሰግድ)ሰው ፍርድና ሰላት የማይሰግድ ሰው የሚጠብቀው ከባድ ክሳራ በሚመለከት ሸክ ሞሐመድ ሷልህ አልኡሰይምን የቀረበ አጭር ማብራርያ ነው ::

    ሰላት የተወ (የማይሰግድ) ሰው ፍርድ

    ዝግጅት ፦ ሼኽ ሙሐመድ ቢን ሳሊህ አልዑሰይሚን

    ትርጉም ፦ መሐመድ ሐሰን ማሜ

    ምስጋና ለአላህ ይገባው ፤ የአላህ ሰላትና ሰላም በመልእክተኛችን ሙሐመድ፤ በቤተሰባቸውና በባልደረቦቻቸው ላይ ይስፈን ::

    ውድ ሙስሊም ወንድሜ ሆይ ! ይህ ለሼኽ ሙሐመድ ቢን ሳሊህ አልዑሰይሚን (አላህ ይዘንላቸውና ) የቀረበ ጥያቄና የሰጡት ምላሽ ነው ::

    ጥያቄ ፦ አንድ ሰው ቤተሰቦቹን ሰላት እንዲሰግዱ ቢያዛቸውና ባይሰሙት : ከነርሱ ጋር አብሮ መኖር ነው ያለበት ወይንስ ቤቱን ለቆ መውጣት ?

    መልስ ፦ እነዚህ ቤተሰቦች በጭራሽ የማይሰግዱ ከሆኑ ከሃዲያንና ከኢስላም የወጡ ናቸው ማለት ነው :: ስለሆነም ከእነሱ ጋር አብሮ መኖር አይችልም :: ነገር ግን ለነርሱ በተደጋጋሚ ጥሪ ሊያደርግላቸው ይገባል በርሱ ላይም ግዴታ ነው :: ምክንያቱም በቁርኣን ፤ በሀዲስ፤ በሰሃቦች ንግግርና በትክክለኛው ሚዛን መሰረት ሰላት የተወ (የማይሰግድ)ሰው ­አላህ ይጠብቀንና ­ ካፊር ነውና ::

    ቁርኣናዊ ማስረጃ

    አላህ ሙሽሪኮችን(በአላህ ላይ የሚያጋሩትን) በማስመልከት እንዲህ ብሏል :

    " فَإِن تَابُوا وَأَقَامُوا الصَّلوة وَءَاتَوُا الزَّكَوةَ فَإِخْوَانُكُمْ في الدِّينِ " التوبة 11.

    " ከተፀፀቱ ፤ሰላትንም ከሰግዱ ዘካንም ከሰጡ የሃይማኖት ወንድሞቻችሁ ናቸው " አት_ተውባህ_11

    አንቀጹ የሚያስገነዝበው ቁም ነገር እነዚህን ተግባራት ካልፈፀሙ ወንድሞቻችን እንደማይሆኑ ነው :: እስላማዊ ወንድማማችነት ከኢስላም በሚያስወጣ የክህደት ተግባር ቢሆን እንጂ በማንኛውም ትልቅ ወንጀል ቢሆንም እንኳ በቀላሉ አይፈርስም ::

    ሃዲሳዊ ማስረጃ

    የአላህ መልእክተኛ (ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም)እንዲህ ብለዋል :

    " بَيْنَ الرَّجُلِ وَبَيْنَ الكُفْرِ وَالشِّرْكِ تَرْكُ الصَّلاَةِ " رواه مسلم .

    " በሰውየውና በክህደት እንዲሁም በማጋራት መካከል ያለው ልዩነት ሰላት ነው" (ሙስሊም ዘግበውታል): ቡረይዳህ (ረድየ ላሁ ዐንሁ)ባስተላለፈው ሀዲስ ላይም እንዲህ ብለዋል :-

    " العَهْدُ الذِّي بَيْنَنَا وَبَيْنَهُمْ الصَّلاَةُ ، فَمَنْ تَرَكَهَا فَقَدْ كَفَرَ " رواه الترمذي ، وقال : حديثٌ حَسَنٌ صَحِيحٌ.

    :" በእኛ እና በእነርሱ(በከሃዲያን)መካከል ያለው መለያ (ቃል ኪዳን) ሰላት ነው ፤ (ሰላትን)የተወ በእርግጥም ክዷል " (አት_ቲርሙዚ ዘግቦታል)

    የሰሃቦች ንግግር

    ይህን አስመልክቶ ከሰሃቦች አንደበት የተነገሩ መልእክቶች በርካታ ናቸው :

    _ ዑመር (ረድየ አላሁ ዐንሁ) እንዲህ ብሏል፦

    " لاَ حَظَّ فِي الإِسْلاَمِ لِمَنْ تِرَكَ الصَّلاَةَ " .

    : " ሰላት የተወ ሰው በኢስላም ውስጥ ምንም እድል (ድርሻ ) የለውም:: " እድል(ድርሻ ) የሚለው ቃል ጥቅል ቃል ነው :: ስለሆነም አነሰም በዛም በኢስላም ውስጥ ምንም አይነት ቦታ እንደሌለው ያስረዳል::

    _ ዐብዱላህ ኢብኑ ሸቂቅም( ረድየ አላሁ ዐንሁ )እንዲህ ይል ነበር፦

    " كَانَ أَصْحَابُ النَّبِيِّ ﷺ‬ لاَ يَرَوْنَ شَيْئًا مِنَ الأَعْمَالِ تَرْكُهُ كُفْرٌ غَيْرُ الصَّلاَةِ "

    “ የአላህ መልእክተኛ ባልደረቦች ቢተው (ቢቀር) ክህደት ነው ብለው ከሰላት ውጭ የሚቆጥሩት ነገር አልነበረም "

    ከትክክለኛው አእምሯዊ ሚዛን አንፃር

    ከትክክለኛ አእምሯዊ ሚዛን አንፃርም ስንመለከተው ማንኛውም በልቡ ውስጥ ቅንጣት ያክል ኢማን ያለው ሰው የሰላትን ደረጃና አላህ የሰጠውን ቦታ እያወቀ ሰላትን እርግፍ አድርጎ ይተዋል ተብሎ ይታሰባልን?!በፍፁም

    _ ሰላት የተወ (የማይሰግድ)ካፊር አይባልም ( ከኢስላም አይወጣም) ያሉት እንደ ማስረጃነት ያጣቀሷቸውን ሳስተውል ከአራት ሁኔታዎች እንዳማይወጣ ሆኖ ነው ያገኘሁት፦

    1_ በመሰረቱ ለተባለው ጉዳይ አስረጅ አይደለም

    2_ ሰላትን መተው እንደማይገባ በሚያመላክት ባህሪ(ገለፃ)የተገደበ ይሆናል

    3_ አንዷን ሰላት በመተው ዑዝር ()በመስጠት ላይ የተገደቡ ናቸው

    4_ ሰፊ መልእክት ያላቸው ይሆኑና ክህደት( ኩፍር)መሆኑን በሚያረጋግጡ አንቀፆች የተገደበና የተብራራ ይሆናል

    ሰላት የማይሰግድ ካፊር(ከሃዲ) እንደሆነ ግልፅ ከሆነ ፤ ከኢስላም የወጡ ሰዎች ህግጋት ይመለከተዋል ማለት ነው።

    (ሰላት የማይሰግድ ሙእሚን ነው፤ ጀነት ይገባል፤ከእሳት(ከቅጣት) ነፃ ይወጣል እና የመሳሰሉትን የሚያመለክት ማስረጃ የለም። በመሆኑም ሰላት የማይሰግድ " ከሀዲ ነው " የሚለውን “ፀጋን መካድ" ማለት ነው አልያም “መለስተኛ ክህደት ነው" ወደሚለው ግንዛቤ እንድንጓዝ አያደርገንም ።)

    እንዲህ ከሆነ የሚከተሉት ህግጋቶች ይመለከቱታል ፦

    አንደኛ፡ አይዳርም(እርሱን ማጋባት አይቻልም ) ፡የማይሰግድ ሆኖ የጋብቻ ውል ቢፈፀም ጋብቻው ትክክል አይሆንም ፡በዚህ ውልም ባለቤቱ አትፈቀድለትም ምክኒያቱም አላህ (I)የተሰደዱ ሴቶችን አስመልክቶ እንዲህ ብሏልና፦

    فَإِنْ عَلِمْتُمُوهُنَّ مُؤْمِنَاتٍ فَلاَ تَرْجِعُوهُنَّ إِلَى الكُفَارِ لاَ هُنَّ حِلٌّ لَهُمْ وَلاَ هُمْ يَحِلُّونَ لَهُنَّ " الممتحنة – 10.

    " አማኝ መሆናቸውን ካወቃችሁ ወደ ከሃዲያን አትመልሷቸው (ምክኒያቱም) እነርሱ (ሴቶቹ)ለእነርሱ(ለወንዶቹ) የተፈቀዱ አይደሉምና፡እነርሱም (ወንዶቹ) ለእነርሱ አይፈቀዱምና " አልሙምተሒና 10

    ሁለተኛ፡ የጋብቻ ውል ከተፈፀመ በኋላ ሰላት ቢያቆም (ቢያቋርጥ)ጋብቻው ይፈርሳል፤ ባለቤቱም ለእርሱ የተፈቀደች አትሆንም ። ለዚህም ማስረጃ ያለፈው አንቀፅ ነው ።

    ሦስተኛ፡ ይህ ሰው ቢያርድ እርዱ አይበላም ። ለምን ? ከተባለ ? ክልክል ስለሆነ ነው መልሳችን ። በአንፃሩ ደግሞ አንድ አይሁዳዊ ወይም ክርስቲያን ያረደውን መብላት ይፈቀድልናል ። በዚህም የተነሳ የዚህ ሰውዬ እርድ _አላህ ይጠብቀንና _ ከአይሁድና ከክርስቲያን እርድ የከፋ ይሆናል ማለት ነው ።

    አራተኛ፡ መካ ወይም የመካን ክልል አልፎ መግባት አይፈቀድለትም ። ምክኒያቱም አላህ(I)እንዲህ ብሏልና፦

    " يَا أَيُّهَا الَّذِينَ آمَنُوا إِنَّمَا المُشْرِكُونَ نَجَسٌ فَلاَ يَقْرَبُوا المَسْجِدَ الحَرَامَ بَعْدَ عَامِهِمْ هَذَا " التوبة 28.

    " እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አጋሪዎች እርኩሶች ናቸው። ከዚህም ዓመታቸው በኋላ የተከበረውን መስጊድ አይቅረቡ። " አት_ተውባህ፡28

    አምስተኛ፡ ከዘመዶቹ አንዱ ቢሞት ውርስ የመካፈል መብት የለውም። ለምሳሌ ፦ አንድ ወላጅ ሰላት የማይሰግድ ልጅ (ወላጅ ሙስሊም ሆኖ ሰጋጅ ነው ልጁ ግን ሰጋጅ አይደለም) እና ራቅ ያለ የአጎት ልጅ ጥሎ ቢሞት ማነው ሊወርሰው የሚገባው ? ከተባለ

    መልሱ: ወራሽ የሚሆነው የገዛ ልጁ ሳይሆን የአጎቱ ልጅ ነው ። ምክንያቱም የአላህ መልእክተኛ ኡሣማህ ባስተላለፈው ሀዲስ ላይ እንዲህ ብለዋል ፦

    " لاَ يَرِثُ المُسْلِمُ الكَافِرَ وَلاَ الكَافِرُ المُسْلِمَ" متفق عليه .

    " ሙስሊም የሆነ ከሃዲን አይወርስም ፤ ከሃዲ የሆነም ሙስሊምን አይወርስም። " (ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል)እንዲህም ብለዋል ፦

    " أَلْحِقُوا الفَرَائِضَ بِأَهْلِهَا ، فَمَا بَقِيَ فَلِأَوْلَى رَجُلٍ ذَكَرٍ " متفق عليه .

    “ ውርስን ለሚገባው አድርሱ የተረፈውን ቅርብ ለሆነ ወንድ ወገን ስጡ " ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል ።

    ይህ እንደ ምሳሌ የተጠቀሰ ሲሆን ወራሾችን ሁሉ የሚመለከት ነው።

    ስድስተኛ፡ ቢሞት ሬሳው አይታጠብም ፤ አይገነዝም ፤ አይሰገድበትም፤ ከሙስሊሞችም ጋር አይቀበርም ። ምን ይደረግ ከተባለ ፡ ጭር ያለ ስፍራ ይወሰድና ጉድጓድ ተቆፍሮ ከነልብሱ እንቀብረዋለን ። ምክንያቱም ለየት ያለ ክብር የለውምና። በዚህም መሰረት ማንኛውም ሰው የማይሰግድ ዘመድ ከሞተበት መስጅድ አምጥቶ ማሰገድ አይፈቀድለትም ።

    ሰባተኛ፡ የቂያማ ቀን ከክህደት መሪዎች ማለትም ከፊርዐውን፡ከሃማን፤ ከቃሩንና ከኡበይ ኢብኑኸለፍ ጋር አብሮ ይቀሰቀሳል ። ጀነትም አይገባም ፡ ቤተሰቡም ማንም ቢሆን እዝነትንና ምህረትን ሊማፀኑለት አይገባም ። ምክንያቱም ከሃዲ ነው ፤ እንዲሁም አላህ እንዲህ ብሏል ፦

    " مَا كَانَ لِلنَّبِيِّ وَالذِّينَ آمَنُوا أَن يَسْتَغْفِرُوا لِلْمُشْرِكِينَ وَلَوْ كَانُوا أُولِي قُرْبَى مِن بَعْدِ مَا تَبَيَّنَ لَهُمْ أَنَّهُمْ أَصْحَابُ الجَحِيمِ " التوبة 113.

    “ ለመልእክተኛውም ይሁን ለማንኛውም አማኝ የእሳት ጓድ መሆናቸው ግልፅ ከሆነላቸው በኋላ የቅርብ ዘመድ ቢሆኑም እንኳ ለሙሽሪኮች ምህረትን ሊጠይቁላቸው አይገባም ።“ ( አት_ተውባህ 113)᎐

    ውድ ወንድሞቼ ጉዳዩ እጅግ አንገብጋቢና አደገኛ ነው። ከመሆኑም ጋር በጣም የሚያሳዝነው አንዳንድ ሰዎች ይህን ጉዳይ ችላ በማለት የማይሰግድ ሰው እቤታቸው ያስቀምጣሉ ነገሩ ክልክል ሆኖ ሳለ ።

    ሰላት የተወ ሰው ወንድም ሆነ ሴት ፍርዱ ይህን ይመስላል

    ሰላትን የተውክና የዘነጋሃት ሆይ ! የቀረውን እድሜህን መልካም ሥራ በመስራት ተጠቀምበት ፡ ከእድሜህ ምን ያክል እንደቀረህ አታውቅምና ወራት ፤ ቀናት ፤ ሰዓታት ?

    የዚህ ሁሉ እውቀት አላህ ዘንድ ብቻ ነው።

    ቀጥሎ ያለውን የአላህ ቃልን ዘውትር አስታውስ ፡

    " إِنَّهُ مَن يَأْتِ رَبَّهُ مُجْرِمًا فَإِنَّ لَهُ جَهَنَّمَ لاَ يَمُوتُ فِيهَا وَلاَ يََحْيَ " طه - 74

    " እነሆ ከሃዲ ሆኖ ወደ ጌታው የሚመጣ ሰው ለእርሱ ገሀነም አለችለት ፤ በውስጧም አይሞትም ህያውም አይሆን "ጣሃ 74

    እንዲህ የሚለውንም ቃል አስታውስ ፡

    {فَأَمَّا مَنْ طَغَى (37) وَآثَرَ الْحَيَاةَ الدُّنْيَا (38) فَإِنَّ الْجَحِيمَ هِيَ الْمَأْوَى (39)} [النازعات: 37 - 39]

    " የካደ ሰውማ ፤ ቅርቢቱንም ህይወት የመረጠ ፤ ገሀነም እርሷ በእርግጥ መኖሪያው ናት " አልናዚዓት ፡ከ 37_39

    አላህ ለመልካም ነገርና ለጥሩ እድል እንዲያበቃህ ፤ እንዲሁም የተቀረውን እለትህን በእውቀት፤ በስራና በዳዕዋ በሸሪዓ ጥላ ስር የምታሳልፍ ያድርግልህ ስል እማፀነዋለሁ

    ወሰለላሁ ዓላ ነቢዪና ሙሀመዲን ወዓላ ኣሊሂ ወሰሕቢሂ ወሰለም